Sunday, July 29, 2012

“እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን “ ራዕየ ዮሐንስ ምእራፍ ፪ ፥ ፲


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡ አሜን! 

“ካለውና ከነበረው ከሚመጣውም በዙፋኑም ፊት ካሉት ከሰባቱ መናፍስት ከታመነውም ምስክር ከሙታንም በኩር የምድርም ነገሥታት ገዥ ከሆነ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን አሜን!””

“እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን “ ራዕየ ዮሐንስ ምእራፍ  ፪ ፥ ፲

በዘላለማዊ የኪዳን ደም ሊታደገንና ለነፍሳችን ፍጹም እረፍትን ሊሰጠን፡ ወደ ክብሩ ዙፋን ሊያደርሰንና ወደ ቅዱሳን ሕብረት ሊደምረን በቀራንዮ ለቤዛነታችን መስዋዕት የሆነው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ሞት ድረስ ለታመነው ሐዋርያ በፍጥሞ  ደሴት በግዞት ሳለ ወደፊት በቤተክርቲያን ላይ ሊደርስ ስላለው መከራ፦ ስደትና ፈተና  እንዲሁም ለቤተክርስቲያን መሪዎችና ለማህበረ ምእመናን ፦ ከእነርሱ ስለሚጠበቀው ኃላፊነትና ክርስቲያናዊ ግዴታ ምን እንደሆነ በአጽንኦት የሚያመላክት፤ አማናዊ ቃሉን ለሚጠብቁ እና እንደ ፈቃዱም ጸንተው ለሚኖሩት ያዘጋጀላቸው ፍጹም የሆነ ሰማያዊ ክብር እና ጸጋ በማስረገጥ በራዕይ የገለጠለት ምስጢራዊ የትንቢት ቃል ነው።

በራዕየ ዮሐንስ ምዕራፍ ሁለት እና ሦስት የተጻፉት ትንቢታዊ መልዕክቶች በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን በእስያ (በዛሬዋ የቱርክ ክፍለ ግዛት) አካባቢ በቅዱሳን ሐዋርያት ትምህርት የተመሰረቱ እና ታላቅ መንፈሳዊ አገልግሎት ይሰጥባቸው የነበሩ ሰባት አብያተ ክርስቲያናት ፦ የአገልግሎት ጥንካሬ እና ድክመት ምን እንደሆኑ በዝርዝር ከማስረዳታቸውም ባሻገር የእነዚያ አብያተ ክርስቲያናት መሪዎች እና  ምእመናን በተለያዩ ምክንያቶች በወቅቱ ከደረሱባቸው ወደ ፊትም ሊመጡባቸው ከሚችሉ ፈተናዎች እና መከራዎች እንዴት ማምለጥ እንደሚችሉ ከእግዚአብሔር የተላከላቸውን መልዕክት ሰምተው፦ በእምነትም ጸንተው፦ በመንፈሳዊ ተጋድሎ በርትተው በእግዚአንሔር ኃይል እና መንፈስ በመታገዝ በአሸናፊነት መጓዝ የሚችሉባቸውን መንገዶች የሚያሳዩ መልዕክቶች ናቸው። ለዚህም ነው በእያንዳንዷ መልዕክት መዝጊያ ላይ “ መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን  ጆሮ ያለው ይስማ።” በማለት ያሳሰበው።

ከሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት መካከልም ከወቀሳው ቃል የዳኑት ሰምርኔስ እና ፊላዴልፊያ  ሲሆኑ የአምስቱ አብያተ ክርስቲያናት አለቆች እና  ምዕመናን ወቀሳ እና ተግሳጽ ደርሶባቸዋል። “እስከሞት ድረስ የታመንህ ሁን.....” የሚለው ቃል በወቅቱ የተነገረውም በሰምርኔስ ቤተ ክርስቲያን ተሹሞ ለነበረው ለቅዱስ ሄሬኔዎስ ነው። በእርሱ እና በምእመናን ላይ እስራት እና  ጽኑ የሆነ መከራ እንደሚደርስባቸው እያሳሰበ በዚህ ሁሉ ግን ሊደርስባቸው በሚችለው ነገር ሳይሳቀቁ ፍርሃትን በእምነት አስወግደው እስከ ሞት ድረስ እግዚአብሔርን በመታመን እንዲጸኑ፦ ይህንን ቢያደርጉ የሕይወትን አክሊል እንደሚቀዳጁ በማስረገጥ ነው መልዕክቱን ያጠቃለለው።

Monday, July 16, 2012

ቤተክርስቲያን እንዴት ተመሠረተች ? ክፍል ፩


 ስለ ክርስትና ሃይማኖት ስለ ቤተክርስቲያን በምንናገርበት ጊዜ ሁሉ ትዝ የሚለንና የምናስተውለው የመጀመሪያው ሰው የአዳም ሁኔታ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን እግዚአብሔር ሁላችንን አባት አዳምን በአርአያውና በመልኩ ከፈጠረው በኋላ ባረከው፡፡ ኹሉንም እንዲገዛ ሥልጣን ሰጠው፡፡ በረከቱን ሥልጣኑንና ሲሳዩን ከሰጠው በኋላ ፈጣሪውን የሚያስታውስበት ትእዛዝ አዘዘው፡፡ እሱ ግን በተሳሳተ ምክር ተመርቶ ከፈጣሪው ትእዛዝ ወጣ፡፡ በዚህ ጊዜ የሞት ፍርድ ተፈረደበት፡፡ ይህም የሞት ቅጣት ለርሱ ዐቅም ቀላል አልነበረም፡፡ በሱም ብቻ አልቀረም የልጅ ልጆቹ ይህን የሞት ቅጣት በውርስ ተካፈሉት፡፡ የዚህ የሞት ጽዋ ተካፋዮች ሆኑ፡፡ የአዳም ሕግን መተላለፍ የልጆቹም ተባባሪነት በእግዚአብሔርና በነሱ መካከል ያለውን ልዩነት እያሰፋው ሔደ፡፡ የፈጠራቸው እግዚአብሔርን ዘንግተው የሰማይና የምድርን ሠራዊት ማምለክ ጀመሩ፡፡ በጨረቃ፣ በፀሐይና በከዋክብት፣ በእሳት፣ በውኃ፣ በእንስሳትና በአራዊት፣ በዛፍና በተራራ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የሰውን ዘር ጨርሶ ለመደምሰስ ስላልፈለገ ይህን የሰው ልጅ መራራና አሰቃቂ ታሪክ ከመጀመሪያው ጀምረው ሲከታተሉ የነበሩ በአንድ አምላክ በማመን የታወቁ ጥቂት ሰዎችን አተረፈ፡፡ እነሱም ከአበው ሄኖክን፣ ኖህን፣ አብርሃምንና ሎጥን ሌሎችንም የመሳሰሉትን ነው፡፡ 

ቤተክርስቲያን እንዴት ተመሠረተች ? ክፍል ፪


ርዕሰ አድባራት አክሱም ጺዮን

 ሕዝቡ በጠቅላላ ገበሬውም ሆነ ነጋዴው የመንግሥትም ባለሥልጣን በሚሠራው ሥራ ሁሉ ባለጸጋ ስለነበር የሮም ግዛት ተወዳዳሪ የሌላት ታላቅ አገር ነበረች፤ ታዲያ ምን ያደርጋል እነዚህ ሁሉ ሀብታት ለሕዝቡ ደስታና ውስጣዊ ዕረፍትን ሊያገኙለት አልቻሉም፡፡ ሁልጊዜ በአካባቢው ከሚሰማው የሽብርና የሁከት ድምጽ የተነሳ ባልታሰበ ቀን እንደመስሳለን በሚል ቀቢጸተስፋ ገዝቶት ነበር፤ ያመልኳቸው ከነበሩ ጣዖታትም አንዳችም የተስፋ ድምጽ አልነበረም፡፡ በቀቢጸ ተስፋ ባሕር ውስጥ ገብቶ የሚማቅቀውና መውጣትም የተሳነው አማኛቸውን ሊያረጋጉት አልቻሉም፡፡ ዳዊት እንደተናገረው ዓይን እያላቸው የማያዩ፤ ጆሮ እያላቸው የማይሰሙ፤ እጅ እያላቸው የማይዳስሱ አፍ እያላቸው የማይናገሩ፤ እግር እያላቸው የማይሄዱ ግዑዛን ናቸውና፡፡ ከዚህም የተነሣ ማለት የሚያመልኳቸው ጣዖታት ሊያረጋጓቸውና ሊረዷቸው ስላልቻሉ ሕዝቡአማልክቶቻችን የዋሃንና ግድ የለሾች ናቸውእያሉ በጣዖታቱ ይዘብት ነበር፡፡ የሰው ልጅ ሥልጣኔም በክፋትና በደግነት መካከል የለውን ልዩነት ለማመልከት አልቻለም፡፡ በዚህም አኳኻን ስለ ሰው ልጅ የወደፊት ዕድል ምንም የተስፋ ጭላንጭል አልነበረም፡፡

Thursday, July 5, 2012

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የቤተክርስቲያን ትምህርት፤ (ክፍል፦ ፬)



ቅዳሴ ማርያምን በመንፈስ ቅዱስ ምሥጢር ገላጭነት የደረሰ አባ ሕርያቆስ ዘሀገረ ብህንሳ ነው። ሕርያቆስ ማለት፦ ለሹመት መርጠውታልና፥ ኅሩይ (ምርጥ) ማለት ነው። አንድም፦ ረቂቅ ምሥጢረ ሥላሴን ይናገራልና፥ ረቂቅ ማለት ነው። እርግጥ ከሊቃውንት ምሥጢረ ሥላሴን ያልተናገረ ባይኖርም፥ እርሱ አምልቶ አስፍቶ ተናግሯል። አንድም፦ አብ ፀሐይ፥ ወልድ ፀሐይ፥ መንፈስ ቅዱስ ፀሐይ ብሎ ጽፏልና ፀሐይ ማለት ነው። አንድም፦ የምዕመናንን ልቡና በትምህርቱ ብሩኅ ያደርጋልና፥ ብርሃን ማለት ነው። አንድም፦ ንብ የማይቀስመው አበባ እንደሌለ፥ እርሱም የማይጠቅሰው ሊቅ የለምና ንብ ማለት ነው። 

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ፦ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት(ክፍል ፫)

፪፦ በውዳሴ ማርያም ትሰብከዋለች።
ካለፈው የቀጠለ . . .

፪፥፫፦ ነፃነትን ሰበከላቸው፤
አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን በግብርናተ ዲያብሎስ ተይዘው (የዲያብሎስ ባሮች ሆነው) ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን፥ እስከ ልጅ ልጆቻቸው በሲኦል ኖረዋል። ኑሮውም የሥቃይና የፍዳ ነበር፥ ይህም ያን ዘመን፥ ዘመነ ፍዳ፣ ዘመነ ኲነኔ አሰኝቶታል። ጊዜው ሲደርስ (እግዚአብሔር፦ አምስት ቀን ተኲል ሲፈጸም፥ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ብሎ ለአዳም የገባው ቃል የሚፈጸምበት ዘመን ሲደርስ) ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ፥ በተለየ አካሉ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከድንግል ማርያም ተወለደ። ቀስ በቀስ አድጎ በሠላሳ ዓመቱ ተጠመቀ፥ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌልን አስተማረ፥ ተአምራትንም አደረገ፥ በመጨረሻም በዕፀ መስቀል ተሰቅሎ (ሥጋውን በመቁረስ፥ ደሙን በማፍሰስ፥ ነፍሱንም በፈቃዱ አሳልፎ በመስጠት) የሰውን ልጅ አዳነ። በአካለ ሥጋ ወደ መቃብር ወርዶ ሙስን መቃብርን አጠፋ፥ በአካለ ነፍስ ደግሞ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ማረከ፥ ሲኦልን ባዶ አስቀረ። ይኽንንም ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ፦ «ክርስቶስም ስለ ሰው ኃጢአት አንድ ጊዜ ሞቷልና፤ ጻድቅ እርሱ እኛን ወደ እግዚአብሔር (ወደ ባሕርይ አባቱ ወደ አብ፥ ወደ ራሱ እና ወደ ባሕርይ ሕይወቱ ወደ መንፈስ ቅዱስ) ያቀርበን ዘንድ ስለእኛ ስለ ኃጢአታችን በሥጋ ሞተ፤ (በተለየ አካሉ በተዋሕዶ ሰው ኹኖ ሞተ) በመንፈስ ግን (በመለኰት) ሕያው ነው። በእርሱም (ሥጋን ተዋሕዶ በአካለ ሥጋ ወደ መቃብር እንደወረደ፥ ነፍስንም ተዋሕዶ በአካለ ነፍስም) በወኅኒ (በሲኦል) ወደአሉ ነፍሳት ሄዶ ነጻነትን ሰበከላቸው።» በማለት ገልጦታል። ፩ኛ ጴጥ ፫፥፲፰-፲፱። ይኽንን ታላቅ የነገረ ድኅነት ምሥጢር ይዘን ወደ ውዳሴ ማርያም ስንሄድ፦ «ፈቀደ እግዚህ ያግዕዞ ለአዳም ኅዙነ ወትኩዘ ልብ ወያግቦዖ ኀበ ዘትካት መንበሩ፤ ጌታ ልቡ ያዘነና የተከዘ አዳምን ነፃ ያወጣውና ወደ ቀድሞው ቦታው (ወደ ጥንተ ርስቱ ገነት) ይመልሰው ዘንድ ወደደ፤» ይለናል። (የሰኞ . ) በተጨማሪም፦ «በዳዊት አገር የተወለደ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምንና ሔዋንን ነፃ አደረጋቸው፤» እያለ ይሰብከናል። (የሰኞ . )

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ፦ የቤተክርስቲያን ትምህርት (ክፍል ፪)


፪፦ በውዳሴ ማርያም ትሰብከዋለች፤

             ውዳሴ ማርያም፦ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ፥ ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ከፈጣሪ በታች ሆና  ለምትከብር ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም ያቀረበው ምስጋና ነው። ሊቃውንት የቤተክርስቲያንን ትምህርት ገና በሕፃንነት የሚጀምሩት ከውዳሴ ማርያም ነው። (ንባቡን ቃል በቃል ማጥናት የሚጀምሩት በአምስት እና በስድስት ዓመታቸው ነው) የዜማውንም ትምህርት እስከ ድጓ ድረስ የሚዘልቁት፦ «ሰላም ለኪ፤» ብለው ከውዳሴ ማርያም ዜማ ጀምረው ነው። የዚህንም ጣዕሙን የሚያውቁት በውስጡ ያለፉ ሰዎችና ሲነገራቸው የሚገባቸው ሰዎች ብቻ ናቸው። አልፎ ሂያጅ መንገደኛ ግን አይገባውም። በውስጡ አልፈውም በዕውቀት ብቻ የቀረባቸው፥ ከሰውነታቸው ያልተዋሐዳላቸው፥ ምሥጢሩ የተሰወረባቸው፥ ማሩ  የመረረባቸው፥ ወተቱ የጠቆረባቸው፥ «ነአኲተከ» እንኳ ካላሉት መናፍቃን፥ ዕድል ፈንታቸው ጽዋ ተርታቸው የሆነባቸውም ጥቂቶች አይደሉም። የጥንቶቹ መናፍቃን ቢያንስ የተማሩ ናቸው፥ ነገር ግን በዕውቀታቸው ሲመጻደቁ አጓጉል ፍልስፍና ውስጥ እየገቡ በትዕቢት ምክንያት፦ ትርጓሜው፥ ምሥጢሩ እየተሰወረባቸው ተስነካክለዋል።

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ፦ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት፤ (ክፍል ፩)


ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት፤ ምክንያቱም የአንድ የክርስቶስ አካል ናትና። ይህች የክርስቶስ አካል የሆነች ቤተ ክርስርስቲያን መሠረቷም ጉልላቷም ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ይህንንም ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ፦ «እርሱም (ክርስቶስ)ከሁሉ በፊት ነው፤ (ለዘመኑ ጥንት የሌለው ቀዳማዊ ነው). . . እርሱም የአካሉ ማለትም የቤተ ክርስቲያን ራስ ነው፤. . . እርስዋም አካሉና ሁሉን በሁሉ የሚሞላ የእርሱ ሙላቱ ናት፤» ሲል ገልጦአታል። ኤፌ ፩፥፳፫፣ ቈላ ፩፥፲፰። በተጨማሪም በቆሮንቶስ መልእክቱ ላይ «የእግዚአብሔር ጸጋ እንደተሰጠኝ መጠን እንደ ብልሃተኛ የአናጺ አለቃ መሠረትን መሠረትሁ፥ ሌላውም በላዩ ያንጻል። እያንዳንዱ ግን በእርሱ ላይ እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ። ከተመሠረተው በቀር ማንም ሌላ ሊመሠርት አይችልምና፤ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።» ብሎአል። ፩ኛ ቆሮ ፫፥፲-፲፩።