Monday, April 1, 2013

ማኅበረ በዓለወልድ ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመተባበር የአርባምንጭ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም የአብነት ት/ቤት ግንባታ ሊያስገነባ ነው

የመሰረት ድንጋዩ በተጣለበት ቦታ

በPDF ለማንበብ እዚህ ይጫኑ 
መጋቢት ፲፭ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም. በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የማኅበረ በዓለወልድ ሰሜን አሜሪካ አህጉረ ስብከት ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመተባበር በጋሞጎፋ ሃገረ ስብከት በአርባ ምንጭ ደብረጽዮን ቅድስት ማርያም ገዳም ያአብነት ትምሕርት ቤት ግንባታ የመሰረት ድንጋይ በሃገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ አማካኝነት የመሠረት ድንጋዩ ተጥሏል።

የፕሮጀክቱ ስም:
ለጋሙጎፋ ሀገረ ስብከት በአርባ ምንጭ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ገዳም የአብነት ትምሕርት ቤት
ግንባታ።


የፕሮጀክቱ ባለቤት: የጋሙጎፋ ሀገረ ስብከት
የፕሮጀክቱ ዓላማ:
·        የመማሪያን የማደሪያ ቤቶችን በመገንባት የውስጥ መገልገያ ቁሳቁስ በማማላት ለመማር ማስተማር ሂደት ምቹ ሁኔታን በመፍጠር 40 ካህናት በሁለት ዓመት ውስጥ ማፍራት በቀጣይም ቁጥሩን ወደ 100 ማሳደግ።
·        ብቁ አገልጋይ ካህናትን በማፍራት አብያተ ክርስቲያናትን እንዲከፈቱና ምዕማናን አገልግሎት እንዲያገኙ ማድረግ፡
·        በመጀመሪያው ዙር ትምህርት የቤተ መቅደስ አገልግሎትና ስብከተ ወንጌል መስጠት የሚችሉ 40 ካህናትን በሁለት ዓመት ውስጥ ማስመረቅ፡

አስፈላጊነቱ: ከ309 አብያተ ክርስቲያናት መካከል በካህናት እጥረት የተነሳ 193 ወይም 63% በመዘጋት ላይ ወይንም በቅርብ ሊዘጉ የተቃረቡ በመሆናቸው።
የፕሮጀክቱ ይዘት: ለአብነት ተማሪዎችና መምህራን የመኖሪያ ቤት፣ የጉባኤ ቤት፣ የምግብ ማብሰያ ቤት ግንባታና የውስጥ እቃዎችን ማሟላት ያጠቃልላል
የፕሮጀክቱ አስፈጻሚ: በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት ማካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የአርባ ምንጭ ማዕከል፥ ከማኅበረ በዓለወልድ ሰሜን አሜሪካ አህጉረ ስብከት ጋር በመተባበር።
ጠቅላላ የፕሮጀክቱ ወጪ:  1.3 ሚሊዮን ብር
 
የመሰረት ድንጋዩ በተጣለበት እለት 
ይህ በማኅበረ በዓለወልድ የገንዘብ እርዳታ እንዲሁም በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት የሚገነባው የአብነት ትምሕርት ቤት ስራው ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ ሲጨርስ አጠቃላይ ፕሮጀክቱ የሚያካትታቸው ስራዎች:
·        የአብነት ተማሪዎች የመኖሪያ ቤት ስራ
ለአብነት ተማሪዎች የመኖሪያ ቤት የሚያገለግሉ ስፋቱ 20 x 4 ሜትር የሆኑ በ5 ክፍሎች የተከፈለና 1.20 ሜትር በረንዳ የሚኖረው ይሆናል። ቤቱ ውሃ ልክ ያለው፣ ከእንጨትና ከጭቃ የሚሰራ፣ ወለሉ በሲሚንቶ ሊሾ የሆነ፣ ከአቡጀዲ የተሰራ ኮርኒስ ያለው፣ በርና መስኮት ከብረትና ከላሜራ የተሰራ፣ ግድግዳው በውጥና በውጪ በሲሚንቶ የተለሰነና ቀለም የተቀባ ሆኖ ይሰራል። እያንዳንዱ ቤት 4 ተደራራቢ አልጋ የሚይዝ ሲሆን 5ቱ ክፍሎች 40 ተማሪዎችን መያዝ ይችላሉ ማለት ነው።
·        የአብነት መምህራን ማረፊያ ቤት ስራ
ለአብነት መምህራን ማረፊያ መኖሪያ ቤት የሚያገለግሉ ስፋቱ 12 x 4 ሜትር የሆኑ በ4 ክፍሎች የተከፈለና 1.20 ሜትር በረንዳ የሚኖረው ይሆናል።
·        የጉባዔ ቤት (የመማሪያ ክፍል) ስራ
የሚሰጠው ትምህርት በአብዛኛው ዜማ እንዲሁም ቅኔና አቋቋም በመሆናቸው የሚሰሩት ሁለት ጉባኤ ቤቶች ለእነዚህ ትምህርቶች የሚያገለግሉ ይሆናሉ። የጉባኤ ቤቶቹ በአርባ ምንጭና በአካባቢው ተወዳጅነት ያለው ክብ፣ ግማሽ ግድግዳ /ቱኩል/ ቤት፣ የውሃ ልክ ያለው፣ ወለሉ ሊሾ ግማሹ የግድግዳው ክፍል በአካባቢው ከሚገኝ ቀርከሃ የሚሸፈን ሲሆን ጣሪያው ውሃ እንዳያስገባ ሸራ ተለጥፎ ባሳር ክዳን የሚሸፈን ይሆናል። ጉባኤ ቤቶቹም በአንድ ጊዜ ቢያንስ 32 ተመሪዎችን የሚይዙ 21 ካሬ ሜትር ስፋት ያላቸው ሆኖው ይሰራሉ። የጉባኤ ቤቶቹ እንደ አስፈላጊነቱ ከመደበኛው የአብነት ት/ቤት ባሻገር የሚሰጥ የስብከት ዘዴና ሌሎች ኮርሶችን፣ የማኅበር ጸሎትና የጽማ መርሐግብሮችን፣ ስብሰባዎችን ለማከናውን የሚያስችል ይሆናሉ።
·        የምግብ ማብሰያ ቤት ስራ
የምግብ ማብሰያ ቤቱ በአንድ ጊዜ 10 ተማሪዎችን ቆመው ምብባቸውን ማብሰል የሚያስችል፣የላይኛው ክፍል ለጭስ መውጫ እንዲመች ክፍት ሆኖ ቀሪው የቤቱም አሰራር ከላይ ለተማሪዎቹ መኖሪያ ቤት ከላይ እንደተገለጸው ይሆናል።
የአርባ ምንጭ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን
·        የልብስ ማጠቢያ ገንዳ ግንባታ
የልብስ ማጠቢያ ገንዳው በአንድ ጊዜ 4 ተማሪዎችን ልብስ ለማጠብ የሚያስችል ሆኖ የሚገነባ ሲሆን 1.40 x 1.20 ሜትር ስፋት ኖሮት በኮንክሪት የሚሰራ ይሆናል። ገንዳው ከመጸዳጃ ቤቱ በአንደኛው ግድግዳ በኩል የሚሰራ ሲሆን ከወለል 1.10 ሜትር ከፍታ ይኖረዋል።
·        የመጸዳጃ ቤት ግንባታ
የመጸዳጃ ቤቱ 4.30 x 3.30 ሜትር ስፋት ያለው ሲሆን 4 ሰዎችን በአንድ ጊዜ ለመጸዳጃ አገልግሎት መስጠት፣ ሌሎች 3 ሰዎችን በአንድ ጊዜ የገላ መታጠቢያ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ሆኖ በብሎኬት ይሰራል። ከላይ የተመከትናቸውን ግንባታዎች በሙሉ ለጥበቃ እንዲመች ሆኖ፣ ለጊቢውም ውበት ለመስጠት ዙሪያውን በጥድ ዛፍ የሚተከል ይሆናል።
·        ቁሳቁስ ማሟላት
ለአብነት መምህራንና ተማሪዎች የመኖሪያ ቤቶች ለጉባኤ ቤቱ፣ ለማብሰያ፣ ለምግብ አገልግሎት የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶች በሙሉ ተገዝተው የሚገቡ ይሆናሉ፡ -
·        በእያንዳንዱ የተማሪዎች ማደሪያ ቤት 1 ሜትር x 2 ሜትር የሆነ 4 ተደራራቢ አልጋ፣ 1 x 1 ሜትር የሆነ 1 ጠረጴዛና 2 የእንግዳ ወንበር የሚያስፈልግ ሲሆን ለ8 ተማሪዎች የልብስ ማስቀመጫ የሚሆን ባለ 4 ተካፋች 1.26 X 1.26X0.4 ሜትር የሆነ ከእንጨት የተሰራ 2 ሎከር ይኖረዋል።
·        ለእያንዳንዱ መምህራን 1X2 ሜትር የሆነ 1 አልጋ፣ 1X1ሜትር የሆነ ጠረጴዛ፣ 2 የእንግዳ ወንበር፣ ለልብስ ማስቀመጫ የሚውል ባለ 1 ተካፋች 1.09X.75X.4 ሜትር የሆነ ከእንጨት የተሰራ ሎከር ያስፈልገዋል።
·        ለተማሪዎች መቀመጫ የሚሆን በቤቱ የውስጠኛው ዙሪያ በጣውላ ከቤቱ ጋር አብሮ የሚሰራ ወንበር ሲኖረው ለመምህሩ መቀመጫ ደግሞ 1 የእንግዳ ወንበር የሚቀመጥ ይሆናል።
የአካባቢው ተማሪዎች ከካህናቱ ጋር
መጋቢት ፲፭ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም. የተጣለው የመሰረት ድንጋይ እና የመጀመሪያው ስራ ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ የተፈለገው በጀት ተጠናቆ እስከ ቀረበ ድረስ ስራውን የዛሬ ዓመት መጋቢት ላይ ተጠናቆ እንደሚያስረክቡ የፕሮጀክቱ አስተባባሪዎች የገለጹ ሲሆን፣ ይህ የተጀመረው ስራ እንኪጠናቀቅ ድረስ እያንዳንዱ የቤተክርስቲያን ልጆች የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉ የፕሮጀክቱ አስተባባሪዎች ገልጸዋል።

አነሳስቶ ያስጀመረን የቅዱሳን አምላክ ስራውን በሚፈለገው ጊዜና ሰዓት አጠናቀን ለተገልጋዩ የጋሙጎፋ ምዕመናን እንድናስረክብ የመድኅኒዓለም ቅዱስ ፈቃድ ይሁንልን እንላለን።

ማኅበረ በዓለወልድ ሰሜን አሜሪካ አህጉረ ስብከት

1 comment:

  1. ሁለቱንም ማህበር አግዚአብሄር ያበርታልን ቅንጅቱ ለሌሎችም አርአያ የሚሆን ነው

    ReplyDelete