Friday, February 21, 2014

ምሥጢረ ጥምቀት- ክፍል-2

ሐ-የጥምቀት ምሳሌ በብሉይ ኪዳን

ኖኀና ቤተሰቡ ከጥፋት የዳኑባት መርከብ የአማናዊቱ ቤተክርስቲያን ምሳሌ መሆንዋ በመጽሐፍ ቅዱስ የተረጋገጠ ነው፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሔር በልቡናቸው ያደረው ኖኀና ቤተሰቡ ከጥፋት ሲድኑ እግዚአብሔርን ድምፅ ያልሰሙት የኖኀ ዘመን ለአማናዊው ጥምቀት ምሳሌነት እንዳለው ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ሲገልጽ (ሲያስተምር) #ጥቂቶች ማለትም ስምንት ነፍስ በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኀ ዘመን በቆየ ጊዜ ቀድሞ አልታዘዙም፡፡
ፈሪሃ እግዚአብሔር በልቡናቸው ያደረው ኖኀና ቤተሰቡ ከጥፋት ሲድኑ እግዚአብሔርን ድምፅ ያልሰሙት የኖኀ ዘመን ለአማናዊው ጥምቀት ምሳሌነት እንዳለው ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ሲገልጽ (ሲያስተምር) ‹‹ጥቂቶች ማለትም ስምንት ነፍስ በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኀ ዘመን በቆየ ጊዜ ቀድሞ አልታዘዙም፡፡ ይህም ውኃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድናል፡፡ የሰውነትን እድፍ ማስወገድ አይደለም ለእግዚአብሔር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ›› 1ጴጥ.3÷20-12፡፡
ኖኀና ቤተሰቡ የዳኑባት መርከብ ምሳሌዋ በሆነው በአንዲቱ ቤተክርስቲያን የሚደረገው ጥምቀት ከፍዳ ያነጻናል ከዲያብሎስ ቁራኝነት ያላቅቀናል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ድኀነት በጥምቀት መሆኑን ሲገልጽ ይህም ውኃ ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድናል ብሏል፡፡
2.             ግዝረት 
ግዝረት የእግዚአብሔር ሕዝብ መለያ ምልክት ነበር፡፡ ያልተገረዘ ሁሉ የአብርሃም ልጅ አይባልም ነበር፡፡ ከሕዝቡም ተለይቶ እንዲጠፋ እግዚአብሔር አዝዞ ነበር (ዘፍ.17 ቁ. 14)፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ ማለትም ያልተጠመቀ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገባም፡፡ ጽኑ ፍዳ ወዳለበት ገሃነም ይወርዳል እንጂ፡፡ ምክንያቱም መንግሥተ ሰማይ ካልገባ ያለው ምርጫ ገሃነም መጣል ነውና (ዮሐ.3÷3-6)፡፡ ስለዚህ ግዝረት ለሕዝበ እግዚአብሔር ግዴታ እንደነበረ ሁሉ ጥምቀትም ለክርስቲያኖች ሊፈጽሙት የሚገባ ሃይማኖታዊ ግዴታ ነው፡፡
ግዝረት ሊመጣ ላለው ለጥምቀት ምሳሌው መሆኑን ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስረዳ ‹‹በክርስቶስ ገዛሪነት የኃጢአትን ሕዋስ ሰንኮፍ ቆርጦ በመጣል ሰው ሠራሽ ያይደለ ግዝረትን የተገዘራችሁበት፤ በጥምቀት ከእሱ ጋር ተቀበራችሁ፣ ከሙታን ለይቶ ባስነሣው በእግዚአብሔር ረዳትነትም በሃይማኖት ከእሱ ጋር ለመኖር በእስዋ ተነሣችሁ›› ብሏል (ቈላ.2÷10-12)፡፡
ግዝረት ማለት ከአካል ላይ ሥጋን ቆርጦ መጣል እንደሆነ ሁሉ ጥምቀትም ሐዋርያው እንዳስተማረን የኃጢአትን ሰንኮፍ ከሕይወታችን ቆርጦ መጣል (ማስወገድ) ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን ግዝረት በሰው አማካኝነት የሚፈጸም ሲሆን የኃጢአት ሥሩ ተቆርጠ ተመንግሎ የሚጣልባት ጥምቀት ደግሞ በካህናት አማካኝነት ይፈጸማል፡፡ ዳሩ ግን የኃጢአትን ሰንኮፍ ቆርጦ ከሕይወታችን የሚያስወግደው (የሚጥለው) በስሙ አምነን የተጠመቅንበት መድኃኒተ ዓለም ክርስቶስ ነው፡፡ በሰው እጅ ያልተደረገ በክርስቶስ ገዛሪነት የኃጢአት ሥር ተቆርጦ የሚወገድበት ግዝረት ጥምቀት ነው፡፡
 አንድ ሰው ሲገረዝ ከአካሉ ደም ይፈሳል፡፡ እደዚሁም ሁሉ በክርስቶስ ደም የተዋጀን ክርስቲያኖች ከኃጢአታችን የታጠብንበትን የጌታ ደም በጥምቀት እናገኘዋለን፡፡ ግዝረት ከአንድ ጊዜ በላይ እንደማይሆንና ሊደገምም እንደማይችል ሁሉ ጥምቀትም የማትደገም፣ የማትከለስ አንዲት ናት፡፡ ሁለት ጊዜ መጠመቅ አይቻልም (ኤፌ.4÷5)፡፡ መጠመቅ ከክርስቶስ ጋር በሞቱ መተባበር ነው (ሮሜ.6÷8)፡፡ ጌታ የሞተው አንድ ጊዜ ነውና ጥምቀትም አንድ ጊዜ ነው፡፡
3.             የእሥራኤልባሕረኤርትራንማቋረጥ
ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን እንዲህ ሲል ገልጦታል ‹‹ወንድሞች ሆይ ይህን ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ፡፡ አባቶቻችን ሁሉ ከደመና በታች ነበሩ፡፡ ሁሉም በባሕር መካከል ተሻገሩ፡፡ ሁሉም ሙሴ ይተባበሩ ዘንድ በደመናና በባሕር ተጠመቁ›› (1ቆሮ.10÷1-12)፡፡
እሥራኤል ሙሴን ይተባበሩ ዘንድ በደመናና በባሕር እንደተጠመቁ እኛም አንድነታችን በደሙ ከኃጢአታችን ካጠበን ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር እንዲሆን እንጠመቃለን፡፡ እስራኤል ከዘመናት የባርነት ቀንበር የተላቀቁትና ነፃ የወጡት የኢርትራን ባሕር ተሻግረው ነው፡፡ ከኃይለኛው ከፈርዖን እጅ የዳኑትም የኤርትራን ባሕር ተሻግረው ነው፡፡ የኤርትራ ባሕር ለፈርዖንና ለሠራዊቱ ሞትን ሲያስከትልባቸው ለእስራኤል ግን ሕይወት፣ ደስታ፣ ነፃነትን አጎናጽፏዋቸዋል፡፡
እኛም ለርኵሳን አጋንንት ከመገዛትና ከፍዳ፣ ከመርገም፣ ከዘላለም ሞት፣ ነፃ ምንሆነው በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምነን ስንጠመቅ ነው፡፡ የኤርትራ-ባሕር ለፈርዖንና ሠራዊቱ መጥፊያ እንደሆነ በጥምቀትም አጋንንት ድል ይመታሉ፡፡ ለዚህ ነው በሥርዓተ ጥምቀታችን ተጠማቂው ከተጠመቀ በኋላ ከምዕራብ (ሲዖል) ወደ ምሥራቅ (ገነት) የሚዞረው፡፡
የሶርያ ንጉሥ ሠራዊት አለቃ ንዕማን ከለምጹ የነጻው በዮርዳኖስ ወንዝ ታጥቦ ነው፡፡ በነቢይ በታዘዘው መሠረት በዮርዳኖስ ውኃ ሰባት ጊዜ ብቅ ጥልቅ በማለት ታጥቦ ሥጋው እንደገና እንደ ትንሽ ብላቴና ሥጋ ንጹሕም ሆኖ መመለሱን በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎ እናገኘዋለን (2ነገ.5÷8-14)፡፡
እኛም ከኃጢአት ደዌ የምንነጻውና ያረጀው ሕይወታችን ሊታደስ የሚችለው በጥምቀት ነው፡፡ ስንጠመቅ የክርስቶስ ደም ከኃጢአታችን እንዳጠበን ማረጋገጣችን ነውና፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ሕዝቅኤል በመንፈስ ቅዱስ ተገልጦለት እንዲህ ብሏል ‹‹በውኃም አጠብሁሽ፤ ከደምሽም አጠራሁሽ፤ በዘይትም ቀባሁሽ›› (ሕዝ 16÷9)፡፡
ለጊዜው ይህ አነጋገር በኃጢአት ለተመላችው ለኢየሩሳሌም የተነገረ ቢሆንም ፍጻሜው ግን በኃጢአት ለተበላሸው ለሰው ሁሉ ሕይወት የተነገረ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ‹‹ባንቺ ዘንድ ባለፍሁና ባየሁሽ ጊዜ እነሆ ጊዜሽ የፍቅር ጊዜ ነበር፡፡ እኔም መጎናጸፊያዬን በላይሽ ዘረጋሁ፡፡ ኀፍረተ ሥጋሽንም ከደንሁ፤ ማልሁልሽም፡፡ ከአንቺም ጋር ቃል ኪዳን ገባሁ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፡፡ አንቺም ለእኔ ሆንሽ፡፡›› (ሕዝ 16÷8)፡፡
እግዚአብሔር በምሕረቱ ሰውን በጎበኘበት ወቅት በፍጹም ፍቅሩ ስቦ ነው የሰውን ልጅ ያቀረበው፡፡ ጌታችንም እርቃኑን በመሰቀል የእኛን ከኃጢአት መራቆት አስቀርቶልናል፡፡ የክብር የሕይወት መጎናጸፊያ አጎናጽፎናል፡፡ ስለ እኛ መከራን ተቀበለ፡፡፡ የእርሱ አደረገን፡፡ ‹‹በውኃ አጠብሁሽ›› የሚለው ‹‹ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ መወለድን›› ያስረዳናል፡፡ ይኸውም በጥምቀት ነው፡፡ በጥምቀት ከዘላለም የኃጢአት ባርነት መላቀቃችንን ሲያስገነዝበን ‹‹ከደምሽም አጠራሁሽ›› ብሏል፡፡ በተጨማሪም ጥምቀት በቅብዐ ሜሮን ማኀተምነት እንደሚጸም ‹‹በዘይትም ቀባሁሽ›› በማለት አረጋግጦልናል፡፡ ‹‹አንቺም የእኔ ሆንሽ›› እንዳለው ሁሉ ተጠማቂውም በጥምቀት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፈጸመውን የቤዛነት ሥራ ሁሉ አግኝቶ የእርሱ ወገን መሆኑን ያስረዳል፡፡
መ-የሕፃናት ጥምቀት
አንዳንድ ሰዎች የሕፃናትን ጥምቀት ሲነቅፉና ትክክለኛ ጥምቀትም እንዳልሆነ ሲናገሩ ይሰማሉ፡፡ ተራ ትችት ግን መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት የሌለው ነው፡፡ እነዚህ ክፍሎች ራሳቸው ከአእምሮአቸው አመንጭተው ላስተማሩት ሐሰተኛ ትምህርት መጽሐፍ ቅዱስ ያስተማረው አስመስለው ለማቅረብ ሲሞክሩም ይስተዋላሉ፡፡
ለምሳሌ ያህል #ያመነ የተጠመቀ ይድናል$ የሚለውን በመጥቀስ ‹‹በመጀመሪያ እምነት ይቀድማል፡፡ ለማመን ደግሞ መማር፣ ማወቅ፣ ማገናዘብና አምኜአለሁ ተቀብያለሁ ሊባል ይገባል፡፡ ሕፃናት ግን የሚያውቁት ነገር ስለሌለ አላመኑም ስለዚህ ያላመኑ ሕፃናትን ማጥመቅ ተገቢ አይደለም›› ይላሉ፡፡ ዳሩ ግን ቤተክርስቲያን ወንዶችን በተወለዱ በ4ዐ ቀናቸው ሴቶችን በተወለዱ በ8ዐ ቀናቸው የምታጠምቀው መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርጋ ነው፡፡
ሀ. ሕፃናት የዘላለምን ሕይወት እንዲያገኙ ወላጆቻቸው ናቤተክርስቲያን የሚሹት ነው፡፡
ያለ ጥምቀት ደግሞ ዘላለማዊ ሕይወት አይገኝም፡፡ ጌታ እንዳስተማረው #ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም$ (የሐ.3÷5)፡፡ ስለዚህ ሕፃናት በወላጆቻቸው እምነት የተነሣ የወላጆቻቸውን እምነት የእነርሱ እምነት በማድረግ ገና በሕፃንነት ጊዜያቸው ከእግዚአብሔር መንግሥት ውጭ እንዳይሆኑ ታጠምቃቸዋለች፡፡ ዳሩ ግን ሳይጠመቁ ቢሞቱ ጌታ እንደተናገረው መንግስተ ሰማይን አያዩአትም፡፡ እንደ ጌታ ትምህርት የምንሄድ ከሆነ #ሰው$ ብሎ ባጠቃላይ ሕፃናትን አዋቂዎችን ሁሉ ጨምሮ ተናገረ እንጂ ከሕፃናት በስተቀር አላለም፡፡ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም፡፡
ለ. ሕፃናት በመጠመቃቸው የቤተ ክርስቲያን አባል ስለሚሆኑ የእግዚአብሔር ጸጋ ተከፋዮች ይሆናሉ፡፡
ገና ከሕፃንነታቸው ጀምሮ የቤተ ክርስቲያንን ሕይወት ይለማመዳሉ፡፡ በዚህ ፈንታ ከሕፃንነታቸው ጊዜ ጀምረው ከእግዚአብሔር ጸጋ ተራቁተው የሚያድጉ ከሆነ ለመጥፎ ሕይወት ይዳረጋሉ፡፡
ሐ. ‹‹ሕፃናት ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ አትከልክሏቸው››
እንዲሁም ጌታችን ‹‹ያመነ የተጠመቀ ይድናል›› ሲል በዚያን ዘመን ገና ወንጌል መስበክ በጀመረበት ላሉት ሰዎች የተነገረ ሲሆን ከክህደታቸውና ከጥርጥራቸው ተመልሰው የሚመጡ ሁሉ አምነው መጠመቅ እንዳለባቸው የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ሕፃናት የእግዚአብሔር ልጆች ሊሆኑ እንደሚገባ ጌታችን ሲገልጽ ‹‹ሕፃናት
 ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ተውአቸው አትከልክሏቸው መንግሥተ ሰማያት እንደ እነርሱ ላሉት ናትና›› ብሏል (ማቴ.19÷14)፡፡ በዚህ የጌታ ትምህርት መሠረት ቤተክርስቲያንም የመሪዋንና የመሥራችዋን የክርስቶስን ቃል መርሕ በማድረግ ወላጆቻቸው ታቅፈው ወደ ቤተክርስቲያን ይዘው በመምጣት ተጠምቀው የእግዚአብሔር ልጆች የቤተክርስቲያን አባላት እንዲሆኑ ሲያደርጉ እርሷ ከልካይ አትሆንም፡፡ ጌታ ተውአቸው ይምጡ ልጅነትን፣ ጸጋን፣ በረከትን ያግኙ ብሏልና፡፡
ሕፃናት ንጹሐነ አእምሮ መሆናቸውን ጌታ ሲያስተምር እንደ ሕፃናት ካልሆናችሁ መንግሥተ ሰማይ አትገቡም ብሏል፡፡
መ. መጽሐፍ ቅዱስ ሕፃናት መጠመቃቸውን ያስተምረናል፤
የሚከተሉት ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
1. በእሥር ቤቱ በተደረገው ተአምር የተደነቀውና ወደ ክርስትና እምነት የተሳበው የወኀኒ ጠባቂ ጳውሎስና ሲላስ ካስተማሩትና ካሳመኑት በኋላ ከነቤተሰቡ መጠመቁ ተገልጾአል፡፡ እግዲህ የተሰበከውና ያመነው የወኀኒ ጠባቂው ሲሆን የተጠመቁት ግን ሕፃናትን ጨምሮ መላው ቤተሰቡ ነው (የሐዋ.16÷33)፡፡
2. ልብዋን ጌታ የከፈተላትና ቃሉን አድምጣ ሕይወትዋን ለክርስቶስ የሰጠችው ልድያ ባመነች ጊዜ የተጠመቀችው ብቻዋን ሳይሆን ከመላው ቤተሰብዋ ጋር ነው፡፡ ከቤተሰቡ መካከል ሕፃናት መኖራቸው የማይቀር ነው (የሐዋ.16÷15)፡፡
3. ቅዱስ ጳውሎስ የእስጢፋኖስንም ቤተሰቦች ደግሞ አጥምቄያለሁ በማለት የእስጢፋኖስን መላ ቤተሰብ ማጥመቁን ገልኦአል (1ቆሮ.1÷16)፡፡ እነዚህ የእስጢፋኖስ ቤተሰቦች ሁሉ ትላልቆች ብቻ ናቸውን? ሕፃናት የሉበትም ይሆን?
4. በሐዋ.ሥራ 2 ላይ እንደተገለጸው በበዓለ ሃምሳ ከ3ዐዐዐ ያላነሱ ሰዎች በጴጥሮስ ተሰበኩ፡፡ ከእነዚያ ውስጥ ብዙዎቹ መጠመቃቸው ተገልጿል፡፡ የተጠመቁት ግን ዐዋቂዎች ብቻ መሆናቸውን የሚገልጽ ቃል የለም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሕፃናትን ጥምቀት የሚነቅፍ ባንዱም ክፍል ተጽፎ አናገኝም፡፡
እስከ አሁን እንደተገለጸው መጽሐፍ ቅዱስ የሕፃናትን ጥምቀት ያልነቀፈ ሲሆን በብሉይ ኪዳን የጥምቀት ምሳሌ የነበሩትን ስንመለከት ይበልጥ የሕፃናትን ጥምቀት ትክክለኛነት ያረጋግጡልናል፡፡
ግዝረት የጥምቀት ምሳሌ ነው፡፡ ሕፃናት በተወለዱ በስምንተኛው ቀን ይገረዙ ነበር (ዘፍ. 17÷12)፡፡ እንግዲህ ሕፃናቱ የሚገረዙት በወላጆቻቸው እምነት እንጂ እነርሱ ዐውቀው ግረዙን ብለው አይደለም፡፡
የእሥራኤል ቀይ ባሕርን ማቋረጥ የጥምቀት ምሳሌ መሆኑ በ1 ቆሮ.10÷2 የተገለጸ ሲሆን ባሕሩን ያቋረጡት ዐዋቂዎች ብቻ ሳይሆኑ ሕፃናትም ጭምር ናቸው፡፡ ከባርነት ከፈርዖን አገዛዝ ነፃ የወጡት ሕፃናቱም ጭምር ናቸው፡፡
እሥራኤል ከበኲረ ሞት የዳኑበት የአንድ ዓመት ጠቦት በግ ደግሞ ምሳሌነቱ የጌታ መሆኑ የታወቀ ሲሆን በዚያን ጊዜ በበጉ ደም አማካኝነት ከሞት የዳኑት የታዘዙትን እሺ ብለው የፈጸሙት ዐዋቂዎች ብቻ ሳይሆኑ የእነርሱ ልጆችም ጭምር ናቸው፡፡ እንግዲህ በወላጆቻቸው እምነት ሕፃናቱ መዳናቸውን ልናስተውል ይገባናል፡፡
ስለዚህ ሕፃናት በአእምሮ ባልበሰሉበትና ስለጥምቀታቸው አምነው ተቀብያዋለሁ ሳይሉ የሚደረገው ጥምቀት እውነተኛ ጥምቀት አይደለም የሚሉ በእግዚአብሔር ቃል መሠረት ከላይ እንደተገለጸው ሁሉ መሳሳታቸው የተረጋገጠ ነው፡፡
እግዚአብሔር ሰውን ይመርጣል እንጂ ሰው እግዚአብሔርን አይመርጥም፡፡ ራሱ ባለቤቱ እንዳስተማረው ሁሉ #እኔ መረጥኋችሁ እንጂ እናንተ አልመረጣችሁኝም$ ብሏል (ዮሐ.15÷16)፡፡ ድኀነት በእግዚአብሔር ቸርነት የሚገኝ እንጂ በሰው ትምህርትና ዕውቀት የሚሸመት ወይም የሚገበይ ዕቃ አይደለም፡፡ ስለሆነም ቤተ ክርስቲያናችን ሕፃናትን ማጥመቋ ከመጽሐፍ ቅዱስና ከቀደሙት አበው ባገኘችው ትምህርት መሠረት ነው፡፡
ክፍል -3 ይቀጥላል - ይቆየን

No comments:

Post a Comment